
አስቲ በዚህ መልኩ እንናገር፤ ይህንን ዘገባ የገባው ያልገባው ያስረዳ ዘንድ አደራ ተጥሏል!
ተጀመረ፤
በሽሮሜዳ ውስጥ በርካታ ኢትዮጵያዊነታቸውን የሚንከባከቡ እና ከሌላው ኢትዮጵያዊ ጋር አብሮ መኖር የማንደራደርበት ነው የሚሉ የመኖራቸውን ያህል፤ የሽሮሜዳ ነጻነት ግንባር (ሽነግ) አባላት ደግሞ ሽሮሜዳ ራሷን የቻለች ሀገር ናት ኢትዮጵያዊነት በግድ የተጫነብን ነው ሲሉ ለበርካታ አመታት ሲታገሉ መኖራቸው ይታወቃል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤
በመላው ኢትዮጵያ ጥበበኞች መብታችን ተገፈፈ፣ መንግስት ከጥበባችን ላይ እጁን ያንሳ እያሉ ጥበብ የተሞላበት ተቃውሞ ሲያሰሙ በርካታ ጊዜ አስቆጠረዋል መንግስት ግን በጆሮው ላይ ባለበት ከባድ ህመም የተነሳ ለጊዜው ሳይሆን በቋሚነት ማንንም መስማት አልተቻለውምና ተቃውሞው መፍትሄ አላመጣም፡፡ ጥበበኞቹ ግን ነጋ ጠባ አቤቱታቸውን ከማሰማት አልደከሙም፡፡ በአሁኑ ሰዓት በመላው ኢትዮጵያ ያሉ ፖለቲከኞች እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም ከኢትዮጵያ ጥበበኞች ጎን በመቆም በደሉ እንዲቆም አጥብቀው እየጠየቁ ይገኛሉ፡፡
ይሄ ግን ለሽነጉ ምሁድ ደስ አላሰኛቸውም፤ “በኢትዮጵያ ውስጥ ካለው ጥበበኛ መካከል ሰማኒያ በመቶው የሚኖረው ሽሮሜዳ ነው፡፡ ስለዚህ የጥበበኞች ትግል ከሽሮሜዳ ትግል ተነጥሎ መታየት የለበትም፡፡ በኮልፌም ይሁን በአስኮ የሚኖረው ጥበበኛ የሽነግን ትግል ያግዝ፡፡ ከዛ ነፃ ሽሮሜዳ እንድትኖረን ያድርግ ከዛ እኛ ሰፈር የሚኖር ጥበብ አልባ ሁላ ቀና ሲል በሜንጫ አንገቱን ብለን እንቆርጠዋለን፡፡” ሲሉ ተናገረዋል፡፡
ንግግራቸውን የተከታተሉ ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል የተሰባሰቡ ጥበበኞች የሽነጉን ምሁር በትዝብት አይን ሲመለከቷቸው የነበረ ቢሆንም አንድ የኮተቤ ጥበበኛ ግን ምሁሩን ደግፈው ይሄ ሲምፕል ካልኩሌሽን ነው የኢትዮጵያ ጥበበኞች ትግል እና የሽሮሜዳ ትግል ተለያይተው አይታዩም ብለዋል፡፡
የሆነው ሆኖ፤ የሽነግ ምሁር አዲስ ስትራቴጂ ነድፈው ይፋ አድርገዋል፡፡ ስልቱም በኢትዮጵያ ከሚኖረው ጥበበኛ የበዛው ሽሮሜዳ ስለሚኖር ከሽሮሜዳ የማይወለዱ ጥበበኞች በሙሉ ለጥበበኝነታቸው ከሚታገሉ ይልቅ ለሽሮሜዳ ነፃነት ይታገሉ ከዛ ሽሮሜዳ ነፃ ስትወጣ በመላው ኢትዮጵያ የሚገኝ ጥበበኛ ነፃ ይወጣል ብለዋል፡፡
ሽሮሜዳ ተሳክቶላት ከኢትዮጵያ ብትገነጠል በኮተቤ እና በአስኮ የሚገኝ ጥበበኛ ሽሮሜዳ ተዘዋውሮ እንዲኖር ይደረጋል ወይስ ጥበበኞች ያሉበት አካባቢ በሙሉ የሽሮሜዳ አካል ሆኖ በሽሮሜዳ መንግስት ይተዳደራል የሚለውን ጥያቄ ምሁሩም ደጋፊዎቻቸውም አልመለሱም፡፡
እደግመዋለሁ ይሄንን ዘገባ የገባው ላልገባው ያስረዳ!
By: Abe Tokichaw
No comments:
Post a Comment