
ክርስትናን እሳት የሚያሸንፈው ቢሆን ኖሮ ድምጥያኖስና ዲዮቅልጥያኖስ በተሳካላቸው ነበር፡፡ክርስትናን መግደል የሚያሸንፈው ቢሆን ኖሮ አይሁድና ሮማውያን፣ ኮሙኒስቶችና ማኦኢስቶች ድል በነሡት ነበር፡፡ ክርስትና በቤተ ክርስቲያኖችመቃጠል፣ በቅዱሳት መጻሕፍትም መቆነጻጸል የሚያበቃለት ቢሆን ኖሮ ኔሮንና ትራጃን፤ ዮዲት ጉዲትና ግራኝ ባስቆሙት ነበር፡፡ ክርስትናእሳት ሆኖ በእሳት ውስጥ ማለፍ ነው፡፡ ክርስትና እሳትን እሳት ሆኖ ድል መንሣት ነው፡፡ እዚህ እሳት ላይ ሦስቱ ሕጻናት ተጥለውነበር፣ እዚህ እሳት ውስጥ ቂርቆስና እየሉጣ ተወርውረው ነበር፡፡ ይኼ እሳት ቅዱስ ፖሊካርፐስን በልቶት ነበር፡፡ ክርስትና ግን ይኼው አለ፡፡

ሊያጠፉት የተነሡት ሁሉ ተረት ሆነዋል፡፡ ክርስትና ግን ህያው ሆኖ አለ፡፡ የሠራነውንቤተ ክርስቲያን ያቃጥሉ ይሆናል፣ የሠራነውን ሰማያዊ ቤት ግን አይደርሱበትም፡፡ ንብረታችንን ይወስዳሉ፣ እምነታችንን አያገኙትም፤እኛን ይገድላሉ፤ ነፍሳችን ግን ከዐቅማቸው በላይ ናት፡፡ ይህንን መከራ አስቀድመን የማናውቀው ቢሆን ኖሮ በደነገጥን ነበር፡፡ ነገርግን ክርስቲያን ስንሆን ይህ እንደሚመጣ እናውቅ ነበር፡፡ ‹ተዘጋጅታችሁ ተቀመጡ› ተብለናልና ተዘጋጅተን ነበር፡፡ እኛ ቆንጨራናቦንብ፣ መትረጊስና አዳፍኔ አንይዝም፡፡ እኛ በጠጠር ጎልያድን የሚረታውን ይዘናል፡፡ በጩኸት ሳይሆን በዝምታ ኢያሪኮን የሚንደውንይዘናል፡፡ በሁካታ ሳይሆን በርጋታ የሚሠራውን ይዘናል፡፡ እነርሱ ሲጮኹ ከአጋንንት ጋር ያወካሉ፤ እኛ ግን ዝም ስንል ከፈጣሪያችንጋር እንነጋገራልን፡፡ ዛሬ በምድር ላይ የለኮሱትን እሳት ብዙዎች በሰማይ እነርሱው ይቀበሉታል፡፡
አይቀርም፤ አምላካችንም ዝም አይልም፡፡ እንገደላለን፤ ግን እናሸንፋለን፤ እንቃጠላለን፤ግን እንለመልማለን፡፡ እናጣለን፤ ግን እናገኛለን፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከተቃጠሉት ሕንጻዎቿ በላይ ናትና፡፡
By Daniel kibret
No comments:
Post a Comment